መብራት ለሶስት ቀን አታብሩ – አዲስ ማስጠንቀቂያ ተሰጠ
መብራት ለሶስት ቀን አታብሩ – አዲስ ማስጠንቀቂያ ተሰጠ
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን የትንሳዔ በዓል ወቅት ኃይል በኤሌክትሪክ አቅርቦት በኩል ችግር እንዳያጋጥም የኮርፖሬሽኑ የከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚዎች ለሦስት ቀናት ኤሌክትሪክ እንዳይጠቀሙ አሳሰበ።
ኮርፖሬሽኑ ዛሬ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በላከው መግለጫ እንዳስገነዘበው ከሚያዝያ ዘጠኝ ማለዳ እስከ ሚያዝያ 12 ቀን 2001 ጠዋት ድረስ ባሉት ቀናት አቅርቦቱ እንዳይስተጓል ከፍተኛ ኃይል የሚጠቀሙ ደንበኞች የኤሌክትሪክ ኃይል ሙሉ በሙሉ እንዳይጠቀሙ አስገንዝቧል፡፡
የሲሚንቶና የሲሚንቶ ውጤቶች፣ ብረታ ብረት፣ ጨርቃ ጨርቅና ልብስ ስፌት፣ ቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ የወረቀት፣ የጐማና ፕላስቲክ፣ የኬሚካል፣ እብነ በረድና የጠጠር ማምረቻ ፋብሪካዎች በኮርፖሬሽኑ የሚጠቀሙትን ኃይል መገልገል ማቋረጥ ይኖርባቸዋል።
እንዲሁም የእንጨትና የብረታ ብረት ዎርክሾፖች፣ ጋራዦችና የኮንስትራክሽን ሥራዎች ከፊታችን ዓርብ ጠዋት እስከ ሰኞ ማለዳ ድረስ የኤሌክትሪክ ኃይል ሙሉ በሙሉ እንዳይጠቀሙ ኮርፖሬሽኑ አሳስቧል፡፡
ኮርፖሬሽኑ ማሳሰቢያውን ተግባራዊ ባለማድረግ የኮርፖሬሽኑን የኤሌክትሪክ ኃይል ሲጠቀሙ በሚገኙ ደንበኞች ላይ አስፈላጊውን እርምጃ እንደሚወስድ ማስገንዘቡን ዜና አገልግሎት ዘግቧል፡