ስስስስስ! ዝም በሉ መንግሥት ም/ጠቅላይ ሚኒስትሩን እየበላ ነው!

የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትራችን የአቶ አዲሱ ለገሠ የአያት ስም “ቀረ ኩራት” ነው። እዚህ አሜሪካን አገር ቢመጡ በላስትኔማቸው ይጠሩ ነበር ። ተቃዋሚዎቻቸው ይህን ስም ቢሰሙ “ስምን መልአክ ያወጣዋል” የሚለውን አባባል ይደግሙት ይሆናል። የሆኖ ሆኖ ግን መልአክም ያውጣው ሰይጣን የም/ጠቅላይ ሚኒስትራችን ላስት ኔም ቀረ ኩራት ነው። ታዲያ ምን አዲስ ነገር ተገኝ ይባል ይሆናል። ምንም!

ግን ወሬ ሲጠፋና ነገርንም ነገር ሲያነሳው ይህን እያነሱ መጫወት መች ይከፋል? ለምሳሌ አንድ ጊዜ አቶ መለስ “አዲሱ ካንተኮ አንድ የጎጃም ገበሬ የበለጠ ያስባል” ብለው ባንድ ስብሰባ ላይ ሰድበዋቸው ያውቃሉ ይባላል። አሁን አሁን ግን አይሰድቧቸውም። ምክንያቱም ከአማራው “ትልቁን ሥልጣን” ተሰጥቷቸዋል የተባሉት አቶ አዲሱ ለገሠ ከገጠር ልማት ሚኒስትርነታቸው ተነስተዋል። ግብርናና ገጠር ልማትን ጨምሮ ሶስት የሚኒስቴር መ/ቤቶችን በሥራቸው ያስተዳድሩና ይመሩ ነበር። አሁን ግን ሥራ ባይፈቱም ኃላፊነት የላቸውም። በሚያስጎመዠው ህገመንግሥት መሠረት አቶ መለስ ድንገት ቢሞቱ ወይም ሥራቸውን መስራት የማያስችል እክል ቢገጥማቸው ሌላ እስኪመረጥ ይተኳቸዋል። የአቶ መለስ ሥልጣን ጥቅልል ብላ አቶ አዲሱ ለገሠ እጅ ስትገባ ማሰቡ ራሱ ይዘገንናል። ያ ቀን ከመምጣቱ በፊት ግን አቶ መለስ ራሳቸው ተመልሰውና ዝቅ ብለው አቶ አዲሱን መተካት የፈለጉ መስለዋል። ያንተንም ሥራ እኔ ደርቤ መስራት አያቅተኝምና ጥፋልኝ ከፊቴ አይነት ጨዋታ እየተጫወቱ ይመስላል። እንደ አማራው ታምራት ላይኔ ባይጨክኑባቸው እንኳ ማንም ሰው ሳያስተውል ትንሽ ራቅ ማድረግና አየር ባየር ማሸት ያስፈልጋል። ከዚያ በኋላ ይሄ ከዘመን በኋላ ህሊናው የተገለጠትና ታች ሆኖ የሚያቅራራው አማራው ተፈራ ዋልዋ እንደ እብድ ብቻውን ያወራታል እንጂ ወደላይ ተማክሮ የሚያመጣው ነገር አይኖርም።

በድርጅታቸው ፍቅር የተነደፉትና ፣ አቶ መለስ ሌላውን በሚዠልጡበት ዱላ የሚበረግጉት አቶ አዲሱ ለገሠ ቀረኩራት ግን፣ እንኳን ይቺን ከዚህም በላይ መስዋእትነት ለመክፈል የተዘጋጁ ስለሆኑ ቻይነታቸው ወሰን እንደሌለው መቸም ይታወቃል። ሰሞኑን ግን ከነገር ሁሉ የአማራው ክልል ቁጥር አልተዋጠላቸውም ይባላል። ከተረፈቻቸው ሥልጣን የህዝብና ቤቶች ቆጠራ ኮሚሽን ቦርድ ሰብሳቢ ሆነው፣ የአማራው ክልል ህዝብ ቁጥር ስንት እንደሆነ አለማወቃቸው ወይም እሳቸው ከሚያውቁት ቀንሶ መገኘቱ ያበሳጫቸው መሆኑ ይሰማል። ምክንያቱም እሳቸው በሊቀመንበርነት የሚመሩትና አማራውን ወክላለሁ ባዩ ብአዴን ይህ ነገር እንዴት ነው ብሎ ማጉረምረሙ ተሰምቷል። በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ዴሞክራሲያዊ መስሎ ዋለ ተብሎ ባንድ ወቅት ተረት የወጣለት የኢህአዴግ ፓርላማ እንኳ ሳይቀር አቶ አዲሱን ሞግቶ “የአማራውን ቁጥር የት ከተታችሁት?” በማለት በሌለው ድፍረቱ አፋጧቸዋል ይባላል። አቶ አዲሱ ደግሞ እስከመጨረሻው መከራከር ሲገባቸው ስህተታቸውን አምነው ግድ የለም በድጋሚ ቆጥረን እንመጣለን ማለታቸው እነ አቶ መለስ የወደዱት አመላለስ አልመሰለም። እስኪ አቶ መለስን ጠይቄ ልምጣ ማለት ነበረባቸው። አንዴ ነገር ተበላሽቷልና ግን ቆጠራው እንደገና እንዲካሄድ ኮሚቴ ተቋቁሟል። ከቁጥርና ከክልል ሁሉ አማራውን መቁጠር ለምን እንዳስቸገረ ማወቁ ግን በራሱ ደስ የሚል ጥያቄ ይመስላል። አቶ አዲሱ ለገሠ ቀረኩራት ግን ራሳቸው የሚያዉቁት ቁጥር ቀነሶ መገኘቱን ራሳቸው አስቀድመው የተቃወሙ ቢሆንም ቅነሳው “ከበላይ” የመጣና በኢህአዴጋዊ የድርጅት አሰራር ስምምነት መሠረት የተፈጸመ ስለሆነ ባያምኑበትም ትእዛዙን መፈጸም ነበረባቸው። መቀነሱ ልክ ነው ብለው ማስረዳታቸውም ከዚህ የመነጨ ይመስላል። “እንኳን ያንተን ሥልጣን ቀርቶ እወክለዋለሁ የምትለውን ህዝብ ቁጥር መቀነስ እችላለሁ” የሚል ጡንቻ ያሳዩት አቶ መለስ ዜናዊ፣ የፈለጉትን የማድረግ አቅማቸውን አሳይተዋል። እንደ አቶ መለስና ጓደኞቻቸው እምነት የአማራው ቁጥር የሂሳብ እውነት ሳይሆን ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ነው። ብሄረሰብ ሲባል ሶማሌውም ኦሮሞውም ጉራጌውም ደቡቡም ሰሜኑም እየተነሳ “አማራ ነኝ” የሚል ከሆነ ህዝቡ ሊያስተላልፈው የፈለገው ነገር አለ ማለት ነው። ምን ይሆን?

ለነገሩ እነ አቶ መለስም መእልክቱ ደርሶናል ባዮች መስለዋል። እንኳን ይቺን ጨዋታ.. የአማራ ባንክ የሆነችው አቢሲኒያ ባንክን እናውቃታለን… የሚል ጨዋታ እየተጫወቱ ይመስላል። ሰሞኑን ኑግ ከሰሊጥ ሌቦች ከጤነኞች በተወቀጡበት ዘመቻ የአቢሲኒያ ባንክ ቦርድ አባላትና ትላልቅ “የአማራ” ነጋዴዎች ተሰብስበው በሙስና ስም ወህኒ ወርደዋል። 25 ያህል ይሆናሉ። ከታሳሪዎቹ መካከል ቀደመው የተያዙት አንድ ሁለት ነጋዴዎች በሂሊኮፕተር ሆነው ከ እነ አቶ አዲሱ ለገሠ ጋር ወዲያና ወዲህ ሲሉ ነበር ብሎ አንድ ታማኝ የአገሪቱ ጋዜጣ ከአንድ ወር በፊት ያጫወተንን እናስታውሳለን። የአማራው ክልል ደጋፊ ናቸው ይባሉ የነበሩት እነዚህ “አብዮታዊ ኢንቨስተሮች” ድንገት ከእነ አቶ አዲሱ ለገሠ ጉያ ተነጥለው እስር ቤት ገቡ ሲባል አጋጣሚው ይገርማል። አቶ አዲሱ ለገሠ ቀረኩራትም እዚያ ጠብቁኝ እኔም ትንሽ ቆየት ብዬ እመጣለሁ ብለው እስር ቤት እንደሚገናኙ ቀጥረዋቸው ከሆነ መቸስ ምን ይደረጋል። ከአማራው የመጨረሻውን ሥልጣን አግኝተዋል የሚባሉት አቶ አዲሱ እንዲህ ከሆኑ ከሳቸው ቀጥሎ በቤተመንግሥቱ የቀረ የአማራ “ከፍተኛ” ባለሥልጣን ማን ነበር? ስሙ ጠፋብን እስኪ ደውላችሁ ንገሩን!
ለማናኛውም የህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ካድሬዎች፣ በወያኔዎቹ ክፍፍል ጊዜ መለስን ጓደኞቻቸውን ያዳናቸው የአማራው ብአዴን ነው ብለው ያምናሉ። ስለዚህ ያደረ ቂም አላቸው የሚሉ አሉ። አሁን ደግሞ አቶ መለስ ራሳቸውን ከወያኔዎቹ ለማዳን ብአዴንን አሳልፈው ለመስጠት እየሄዱ ነው ይባላል። የዚች የኤርትራ ነገርኮ መከራ ሆነ። አቶ መለስ ዜናዊ መቸም የሷ ነገር አይሆናቸውም። ለሷ ሲሉ አሳልፈው የማይሰጡት ነገር የለም። አሳልፈው እንዳይሰጡት የሰጋ ሁሉ ማረኝ ብዬሃሉ እሞትብሃለሁ—-ማለቱ አይቀርም መቸም ኩራት ቀርቷል!

Leave a Reply

Photo Gallery

Designed by Nebxstudios