ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዐቃቤ መንበር ፓትርያርክ ሆነው ተመረጡ

(ENA) የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የአርሲ ሃገረ ሰብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዐቃቤ መንበር ፓትርያርክ ሆነው እንዲሰሩ መወሰኑ የሲኖዶሱ ዋና ፀሃፊ ገለፁ።

የሲኖዶሱ ዋና ፀሐፊና የከፋ፣ ሸካና ቤንች ማጂ ዞን አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የፓትርያርኩን ምርጫ አስመልክተው ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ የዋና ፓትርያርክ ምርጫ እስከሚካሄድ ድረስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ዐቃቤ መንበር ፓትርያርክ ሆነው እንዲሰሩ ተወስኗል።

የቤተክርስቲያኒቱ መንፈሳዊም ሆነ ማህበራዊ ተግባራት ዘርፈ ብዙ በመሆናቸው በሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ጳውሎስ ምትክ ጳጳስ መምረጥ ማስፈለጉን ገልጸዋል።

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ዛሬ ባደረገው ስብሰባ ቀደምትነት ካላቸው ብፁዓን አባቶች መካከል ብፁዕ አቡነ ናትናኤልን ላልተወሰነ ጊዜ ዐቃቤ መንበር ፓትርያርክ ሆነው እንዲሰሩ መወሰኑን አመልክተዋል።

ከዐቃቤ መንበር ፓትርያርክ ምርጫ በተጨማሪ ከቋሚ ሲኖዶሱ ጋር አብረው የሚሰሩ ሰባት አባላት መመረጣቸውን ዋና ፀሃፊው ተናግረዋል።

የተመረጡት አባላትም ብፁዕ አቡነ ጢሞቲዮስ፣ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፣ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ፣ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስና ብፁዕ አቡነ አብርሃም መሆናቸውን ገልጸዋል። (ENA ETV)

Leave a Reply

Photo Gallery

Designed by Nebxstudios