ዓረና ትግራይ ናይ አንድነት ፓርቲ ተለጣፊ እዩ – ሕወሓት


ሃይለሥላሴ ተስፋይ
ዓረናና አንድነት ፓርቲ ብሎም መድረክ እስካልጠፉ ድረስ የትግራይ ህልውና አደጋ ላይ ነው በሚል ገዢው ፓርቲ የሐሰት ፕሮፖጋንዳ
እየነዛና በአባላቱም ላይ የከፋ ችግር እየፈጠረ መሆኑ እየተገለጸ ነው። በተለይ ዓረና ትግራይ ለአባላቱና ደጋፊዎቹ ካሰራጨው ጽሁፍ ውስጥ ለምሳሌ ይሄኛው ይገኝበታል።
“ዓረና እውን ምጽላትና ይሠረኽ አሎ ክሻብ ናይ አምሓራ መገልግሊ ባንዳ ዝብል መቀጽልታ ተለጢፍሉ አብ መረጻ 2002 ዘርዒ መሰረ ዝገበረ ናይ ገዛኢ ፓርቲ ፕሮፖጋንዳ ጥቅአት ክወርዶ ጸን ኢዩ”
ዓረና ከጠላቶቻችን ጋር እየሠራ የሚገኝ የአማራ አገልጋይ ባንዳ ነው የሚል ቅጽል በመለጠፍ በ2002 ምርጫ ወቅት ገዢው ፓርቲ የጎሰኝነት ፕሮፖጋንዳ ጥቃት መንዛቱ ይታወቃል….
ኢህአዴግ 96 ከመቶ አሸነፍኩ ባለበት ባለፈው ምርጫ 2002 ላይ በትግራይ ተፎካካሪ ሆነው ከቀረቡት ፓርቲዎች ውስጥ መድረክ ትልቁ ነበር። መድረክን በመወከል በመላው ትግራይ ዕጩዎቹን ያቀረበው ፓርቲ ደግሞ ዓረና ትግራይ መሆኑ ይታወቃል። በአብዛኛው የትግራይ ምሁራንና በቀድሞ የህወሓት ታጋዮች ጭምር የተዋቀረው ዓረና በትግራይ ውስጥ እንቅስቃሴ በሚያደርግበት ጊዜ ገዢው ፓርቲ ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ በትግራይ ውስጥ ዓረናና መድረክን አስመልክቶ ያሰራጫቸው የነበሩ መግለጫዎችና ክሶች አሁንም እንደገና ማንሰራራት መጀመራቸው ይሰማል።
በተለይ ባለፈው ምርጫ “አረና ከጠላቶቻችን ጋር እየሠራ የሚገኝ ባንዳ ነው” የሚሉና “አረና ትግራይ ናይ አንድነት ፓርቲ ተለጣፊ እዩ” በማለት አረና የአንድነት ፓርቲ ተለጣፊ መሆኑን ሲገልጹ ቆይተዋል። ፕሮፖጋንዳው አሁንም ያላበቃ መሆኑን የገለጸው አረና ህወሃት ይህን ሁሉ የሚፈጽመው የኢትዮጵያን ህዝብ ከፋፍሎ ለመግዛት መሆኑን አስታውቋል። በትግራይ ህዝብና በአማራ ህዝብ መካከል መጠራጠርና መቀናቀንን ለመፍጠር የቀለለ መንገድ አድርገው ስለሚወስዱት ነው ብሏል።
ይህ ኢትዮጵያውያንን ከፋፍሎ መግዛት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ታሪክ ውስጥ የቆየ መሆኑን ገልጾ ህብረተሰቡና አባላቱ የዚህ ተጠቂ እንዳይሆኑ አሳስቧል።
ህወሃት በድርጅቶች ላይ ብቻ ሳይሆን በግለሰቦችም ላይ ያነጣጠረ ዘመቻ በመክፈት በተለይም አቶ ስዬ ላይ ሰፊ ዘመቻ ሲያካሂድ መቆየቱን ገልጿል። አቶ ስዬ የአረና አባል አለመሆናቸው እየታወቀ፣ “ አረናን ከኋላ ሆነው የሚመሩት ስዬ ናቸው” በሚል በዚያም ላይ ፍጹም ሐሰት የተሞላበትንና የጎሰኝነት ፖለቲካ ሲያራምድባቸው ቆይቷል። “አይተ ስዬን ወልቃይት ንሁመራንን ጎንደር ክንመልስ ኢሎም ተዛሪቦም እዮም ብዝብል ፀእዳ ሃሶት ተደሪኾም” አቶ ስዬ ወልቃይትና ሁመራን ወደ ጎንደር እንመልስ ብለው ተናግረዋል የሚል የሀሰት ውንጀላ በመርጨት ህዝቡን በሀሳት ለማነሳሳት ሞክረዋል። አቶ ስዬም ጨርሶ ያልተናገሩት የሐሰት ወሬ መሆኑ ቢገልጹም ህወሓት ግን አቶ ስዬን የኢሠፓና የደርግ አባሪ የትግራይ ህዝብ ጠላቶች ተባባሪ አድርገው መክሰሳቸውን አላቋረጡም።
“ናይ አንድነት ፓርቲ ተለጣፊ እዩ” እየተባለ የሚከሰሰው ዓረና ትግራይ የጽንፈኞቹ የአንድነት አባላት ጉዳይ አስፈጻሚ መሆኑን በመግለጽ ህወሃት እየከሰሰ ነው። በጠላትነት የተፈረጁት አባላትና ደጋፊዎቹም የእርዳታ እህል እንዳያገኙ ማድረግ፣ መደብደብ፣ ማሰር፣ ከአገር እንዲጠፉ ማድረግ በአሁኑ ሰዓት በትግራይ ክልልም ሆነ በኢትዮጵያ እየተፈጸመ ያለ በደል መሆኑን ድርጅቱ አመልክቷል።

Leave a Reply

Photo Gallery

Designed by Nebxstudios